ዋልያዎቹ ከዛምቢያ ጋር ባካሂዱት የወዳጅነት ጨዋታ ድጋሚ ተሸንፈዋል
የአቋም መፈተሻ ጨዋታቸውን ከ ዛምቢያ ጋር ያካሄዱት ዋልያዎቹ በመጀመሪያው አጋማሽ በተቆጠረባቸው ሶስት ግቦች ሊሸነፉ ችለዋል ።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሁለተኛ አጋማሽ አንድ ግብ ሲያስቆጥር ተቀይሮ ወደ ሜዳ የገባው ጌታነህ ከበደ የጎሏ ባለቤት ሆኗል ።
ዋልያዎቹ በአቋም መፈተሻ ጨዋታዎች ስድሰት ጎሎችን አስተናግደው ሶስት ጎሎችን ማስቆጠር ችለዋል ።
ከዚህ በተጨማሪም በአሰልጣኝ ውበቱ አባተ ጥሪ ከቀረበላቸው ተጫዋቾች መካከል አንዱ የሆነው የመስመር ተጫዋች ሚኪያስ መኮንን ጉዳት ማስተናገዱ ታውቋል ።
ሚኪያስ መኮንን ከ ዛምቢያው የዛሬ የአቋም መፈተሻ አስቀድሞ ረፋድ ላይ በነበራቸው የልምምድ ጊዜ የጡንቻ መሸማቀቀ ጉዳት እንዳስተናገደ አሰልጣኝ ውበቱ አባተ ገልፀዋል ።
ከሚኪያስ መኮንን በተጨማሪ ከቀናት በፊት ሐሙስ የቡናማዎቹ የፊት መስመር አጥቂ አቡበከር ነስሩ ተመሳሳይ ጉዳት ማስተናገዱን ለማወቅ ተችሏል ።
ከሁለቱ ተጫዋቾች በተጨማሪም የቅዱስ ጊዮርጊሱ የፊት መስመር አጥቂ አቤል ያለው ጉዳት ማስተናገዱ ተሰምቷል ።
በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ከአይቮሪኮስት፣ ማዳጋስካርና ኒጀር ጋር የተመደበው ብሔራዊ ቡድኑ ባደረጋቸው ሁለት ጨዋታዎች በማዳጋስካር ተረትቶ፣ አይቮሪኮስትን 2 ለ 1 በመርታት በሦስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ መገኘቱ የሚታወስ ነው